ሐመርን ያውርዱ
ስምዓ ጽድቅ ያውርዱ
የወሩ የማኅበረ መልእክት
Saturday, 25 September 2021 00:00
የሀገሪቱ መንግሥት የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንንና የምእመናንን ደኅንነት ሊያስጠብቅ እንደሚገባ የምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት የሃማኖት አባቶች ጥሪ አቀርቡ፡፡  በቅርቡ ማለትም ነሐሴ ፲፪ ቀን ፳፻፲፫ ዓ/ም በምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት ኪረሙ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥረ በሚገኙ የገጠር ቀበሌዎች አሸባሪው ፀረ ሰላም ታጣቂ ቡድን በፈጸመው ጥቃት ቁጥራቸው የማይናቅ ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ለሞትና ለስደት መዳረጋቸውን የሃማኖት አባቶቹ አንስተው በተጨማሪም በከፍተኛ ወጭ የተገነቡ በርካታ አብያተ ክርስቲያናት በዝርፊያና በቃጠሎ መውደማቸውን አስረድተዋል፡፡     የሃይማኖት አባቶቹ አያይዘውም “ወቅታዊ የሀገሪቱን የፖለቲካ ቀውስ እንደመልካም አጋጣሚ ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያን ችግር ውስጥ እንድትወድቅ የሚፈልጉ የአንዳንድ ፀረ ሰላም ኃይሎች እኩይ ድርጊት ተዳምሮ ቤተ ክርስቲያንን ከፍተኛ አደጋ ላይ ጥሏታል” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ መንግሥት የምእመናንና የአብያተ ክርስቲያናትን ሰላምና ደኅንነት የመጠበቅ ኃላፊነቱን ሊወጣ እንደሚገባም ጥሪ አቅርበዋል፡፡  “በሀገረ ስብከቱ ሥር  ያሉ ለችግር የተጋለጡ አብያተ ክርስቲያናትንንና ምእመናንን ለመጎብኘት የኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የደኅንነት ድጋፍ እንዲያደርግልን ጥያቄ ብናቀርብም እስካሁን ድረስ ምላሽ አላገኘንም” ሲሉም የሃይማኖት አባቶቹ ቅሬታ አቅርበዋል፡፡ በክልሉ መንግሥት በኩል አልፎ አልፎ ከሚገባው የድጋፍ ቃል  ውጭ ተጨባጭ መፍትሔ ማምጣት እንዳልተቻለም አክለዋል፡፡  የምሥራቅ ወለጋ ሀገረ ስብከት አካባቢ የጦርነት ቀጠና በመሆኑ በዚህ የተነሣ በፀጥታ ችግር ምክንያት ወደ ወረዳው ሀገረ ስብከቱ አጣሪ ልዑክ መላክ አልቻለም ያሉት የሃይማኖት አባቶቹ ይሁን እንጂ ወረዳ ቤተ ክህነቱ የችግሩን ጥልቀትና ስፋት ለኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነትና ለሀገረ ስብከቱ ማሳወቁን አንስተዋል፡፡   ከዚህ ጋር በተያያዘ “በአካባቢው ያገለግሉ የነበሩ ካህናት በመሞታቸውና በመፍለሳቸው የተነሣ ከዚህ ቀደም የነበረው አገልግሎት ተዳክሞና አብያተ ክርስቲያናትም ተዘግተው ይገኛሉ ካሉ በኋላ የሀገረ ስብከቱ የሃማኖት አባቶች በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆነው የግል ጉዳያቸውን የሚያራምዱና ቤተ ክርስቲያንን እያስጠቁ ያሉ አካላት ከድርጊታቸው እንዲቆጠቡም መክረዋል፡፡  የሃይማኖት አባቶቹ አክለውም “የቤተ ክርስቲያንን ውድቀት የሚመኙ በርካታ አካላት መኖራቸውን በመረዳት ለእነዚህ ፀረ- ኦርቶዶክስ ኃይላት ክፍተት መስጠት ተገቢ አይደለም፡፡ በአካባቢው ያለው የፀጥታ ችግር እጅግ ውስብስብና አሳሳቢ መሆኑን መንግሥት ተረድቶ ለቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን አስፈላጊውን ድጋፍ ሊያደርግ እንደሚገባና ቤተ ክህነትም ከመንግሥት ጋር ተነጋግሮ የአካባቢው ፀጥታ እንዲከበር ጥረት ቢያደርግ መልካም ሊሆን እንደሚችል  አስረድተዋል፡፡  በጉዳዩ ዙሪያ ተጨማሪ ማብራሪያ እንዲሰጡን ለኦሮሚያ ክልል ምሥራቅ ወለጋ ዞን ፖሊስ ኮማንደር ታሪኩ ስልክ የደወልንላቸው ቢሆንም ስልክ ባለማንሣታቸው አስተያየታቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡   
Saturday, 25 September 2021 00:00
ብዙዎች በልበ ሙሉነት ‹‹ኢትዮጵያ ሀገረ እግዚአብሔር ናት›› ብለው ሲናገሩ በርካታ ምክንያቶችን በመጥቀስ ነው፡፡ ታሪኳ፣ ሃይማኖታዊ ሥርዓቷ፣ በዓላቷ፣ የሕዝቦቿ አብሮ የመኖር ባህል፣መከባበር፣ እንግዳ መቀበል፣ አለባበስ ስያሜውን እንድታገኝ ካስቻሏት ውስጥ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያውያን ይልቁንም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  ምእመናን የነዚህ መንፈሳዊ ዕሴቶች ባለቤት በመሆን ግንባር ቀደሞቹ ናቸው፡፡ እምነታችን በእነዚህ ዕሴቶች ያሸበረቀ ልዩ መስተጋብር ያለውና በሌሎች ዘንድ በአርአያነት የሚጠቀስ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሃይማኖታዊ ሥርዓት ሀገራችን በዓለም ደረጃ እንድትታወቅ፣ ክፍ ብላም እንድትታይ አስችሏታል፡፡ የዘመን መለወጫው፣ የደመራ፣ የልደት፣ የጥምቀቱና የፋሲካው ክብረ በዓላት የበዓሉ ባለቤት ከሆነው ከኦርቶዶክሳዊው ምእመን አልፈው በሀገሪቱ ላይ የሚፈጥሩት ተጽዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ የሞቁ የደመቁ፣ ግዘፍ ነሥተው የሚታዩ ናቸውና፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሆነች ምእመናን ልጆቿ እነዚህን መንፈሳዊ ዕሴቶች ለመጠበቅ የሚያደርጉት መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ቀላል አይደለም፡፡ በታሪክ የሀገር መሪዎች የነበሩ ነገሥታቱ ሳይቀሩ በግንባር ቀደምነት ይሳተፉባቸው የነበሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች አሻራቸው ሳይጠፋ ዘመናትን ተሻግረው እዚህ ደርሰዋል፡፡ ይህ ከትውልድ ወደ ትውልድ ከአባቶች ወደ ልጆች በቅብብሎሽ እዚህ የደረሰው መንፈሳዊ በዓላችን ከትላንት በሰፋ፣ ባሸበረቀ ለሌሎች መስህብ በሆነ መልኩ ሲከናወን ማየትን ያህል የሚያስደስት ነገር የለም፡፡ ዛሬ ዛሬ እነዚህ በዓላት ከፍ ባለ ደረጃ እንዲከበሩ ከበዓሉ ዋዜማ ጀምሮ ከፍተኛ ዝግጅት በማድረግ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጆች በተለይም ወጣቶች ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ በዓላት ከመድረሳቸው በፊት በየአካባቢው ያሉ ኦርቶዶክሳውያን ወጣቶች አብያተ ክርስቲያናትን፣ መንገዶችን በማጽዳት፣ ሰደቅ ዓላማ በመስቀል፣ ምእመናንን በማስተናገድ፣ ጸበል ጸዲቅ በማዘጋጀት የሚደረገው መንፈሳዊ ርብርብ ቀላል አይደለም፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን ያለን መፈሳዊ ቅንዓት እና ተነሣሽነት በመንፈሳዊ ዕውቀት ላይ የተመሠረተና ፈሪሃ እግዚአብሔር የታከለበት ሲሆን ደግሞ ይበልጥ ጥሩ ነው፡፡ በዚህ ታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት ውስጥ በብዙዎች ሳይሆን በአንዳንዶች ዘንድ የሚታይ እና ነቀፌታን የሚያስከትል አገልግሎት ዘወትር ክርስቲያናዊ ተግባሩ ማድረግ በቤተ ክርስቲያን ስምም ሆነ በአካባቢዋ እንዳይሠራ መከላከል የሁሉም ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ድርሻ ሊሆን ይገባል፡፡ እናት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል፣ የድርሻውን ለመወጣት ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጣውን የቤተ ክርስቲያን ልጅ በመጀመሪያ ቃለ እግዚአብሔርን በማስተማር መንፈሳዊ እንዲሆኑ ማድረግ፣ የሚሰጠውን አገልግሎት መንፈሳዊ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር በዓላትን ጠብቆ መስቀልና ጥምቀት በሚውሉበት ቀን ብቻ  የሚመጣውን ትውልድ ዘወትር ወደ ቤተ ክርስቲያን መሄድ ተገቢ መሆኑን፣ በጾምና በጸሎት ዘወትር ቤተ ክርስቲያን መሳለምና ማስቀደስ በንስሓ ሕይወት ውስጥ መኖርና ከቅዱስ ቁርባን መሳተፍ በሚችሉበት መንገድ ማስተማር የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት ያቀናልና ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ በተለይ የቤተ ክርስቲያን ታላላቅ በዓላት ላይ የሚታዩ የሥነ ምግባር ግድፈቶችን ለማረም ከአገልግሎት በፊት እና በኋላ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል በየዋህነት እና በስመ ኦርቶዶክሳዊነት ደፋ ቀና የሚሉትን ሰብስቦ መሠረታዊ የሆነውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት መስጠት ያስፈልጋል፡፡ በመንፈስ ተጀመርው በሥጋ በሚያልቁ ታላላቅ የቤተ ክርስቲያን በዓላት ላይ በሚደረጉ አገልግሎቶች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግድ ሊላት ይገባል፡፡ ዛሬ ዛሬ ብዙዎች በቤተ ክርስቲያን ስም ተሰባስበው አገልግሎቱን በሥጋዊ መንገድ ሲያከናውኑ ማየት የተለመደ ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ያፈነገጠ ልብስ ለብሰው፣ በአካላዊ ቁመናቸው ፍጹም ዓለማዊ ሆነው፣ በተንጨባረረ ፀጉር በቤተ ክርስቲያን ዐደባባይ ላይ የሚቆሙ መንፈሳዊ አገልጋዮች በመጀመሪያ መንፈሳዊ ማድረግ እና መምከር ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ብሎም ከመንፈሳውያን አባቶችና እናቶች እንዲሁም ወንድሞችና እኅቶች ይጠበቃል፡፡  ታላላቅ የቤተ ክርስቲያንን በዓላትን አስመልክቶ ለሰንደቅ ዓላማ፣ ለጸበል ጸዲቅ፣ ለቄጠማ እየተባሉ ከየምእመናኑ የሚሰበሰቡ በርካታ ገንዘቦች ለታለመላቸው ዓላማ ሳይውሉ ቀርተው የግለሰቦችን ኪስ የሚያደልቡ፣ ከመንፈሳዊነት ባፈነገጠ መልኩ ለመዝናናት፣ ለመጠጥ ሲውሉ ማየት ሥርዓት እየሆነ መጥቷልና ‹‹ሳይቃጠል በቅጠል›› ሊባል ይገባል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ የቤተ ክርስቲያንን ስም የሚያጎድፍ መንፈሳዊ በዓላቱንም የሚያጠለሽ ድርጊት በቤተ ክርስቲያን ዙሪያና በቤተ ክርስቲያን ስም ሲደረግ እያዩ እንዳላዩ አልፎ ሂያጅ ከመሆን ቆም ብሎ ትክክለኛውን ነገር በመንገር እና በመገሠጽ ክርስቲያናዊ ግዴታችንን መወጣት ተገቢ ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ በእነዚህ ታላላቅ በዓላት አገልግሎት ስም በየሰፈሩ የተደራጁ በርካታ ወጣቶችና፣ ማኅበራት ቢኖሩም በትክክለኛው መንገድ ቤተ ክርስቲያንን እየደገፉ ያሉት የትኞቹ ናቸው? የሚለው ግን አጠያያቂ ነው፡፡ ከላይ ለማንሣት እንደሞከርነው መንፈሳዊ ቅንዓቱ ፣ የቤተ ክርስቲያን ፍቅሩ፣ ለአገልግሎት መትጋቱ ቢኖርም አንዳንዶቹ በዓመት አንድ ጊዜ የሚመጡ የመስቀል ወፍ ናቸው፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ምግብና መጠጥ ብቻ የሚያሰባስባቸው የስም ክርስቲያኖች በመሆናቸው እነዚህን ከመንፈሳውያኑ አገልጋዮች ለይቶ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ማስተማር ይገባል፡፡ በቤተ ክርስቲያን በዓላት ስም የሚደረጉ የሠፈር ልዩ ልዩ ዝግጅቶች አቅጣጫቸውን እየሳቱ ነውና በየአካባቢ የምንገኝ የቤተ ክርስቲያን ልጆች አባቶች እና እናቶች ትክክለኛውን መንገድ በማሳየት፣ በማስተማር ማስተካከል ይጠበቅብናል፡፡ ለምሳሌ በየሰፈሩ ወጣቶች እና የአካባቢው ምእመናን ተሰብስበው ደመራ በመለኮስ የመስቀል በዓልን ያከብራሉ፡፡ በዓሉን ለማክበር መሰባሰባቸው እሰይ የሚያሰኝ ቢሆንም ያለ ዕውቀት የሚሄዱትን በማስተማር፣ ዝግጅቱ መንፈሳዊ እንዲሆን ቃለ እግዚአብሔር እንዲሰጥ በማድረግ፣ ከዘፈን ይልቅ መንፈሳዊነቱን ጠብቆ በመዝሙር እንዲሆን ማድረግ በአጠቃላይ በዓላት መንፈሳዊ ዕሴታቸውን እንዳይለቁ ለማድረግ በያለንበት የድርሻችንን ልንወጣ ይገባል፡፡              
Wednesday, 15 December 2021 00:00
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ።                                                 ዘመኑ በጋራ የምንቆምበት ነው    የምንገኝበት ዘመን መከራ የበዛበት በመሆኑ ከመቼውም ጊዜ በላይ መተባበርና መደጋገፍ የሚጠይቅ ነው።መከራ ሲገጥመን መተባበር እንደሚኖርብን የማንም ማሳሰቢያና ማባበያ አያስፈልገንም። በአገራችን እየደረሰ ያለው መከራ ሊያስተባብረን ካልቻል ሌላ የሚያፋቅረን ነገር ማግኘት አንችልም። የምንኖርባትን ዓለም ጣዕም የቀየሩት ራሳቸውን ብቻ ለማትረፍ ሲደክሙ የኖሩት ሳይሆኑ በመተባበር ለመከራ የተዳረጉትን ሰዎች ሕይወት ሲታደጉ የኖሩት መሆናቸውን መገንዘብ ይገባል። ከመለያየት ይልቅ መተባበር፣ ከመቀበል ይልቅ ለተቸገሩት መስጠት የቻሉት የሰው ፍቅር የበለጠባቸው፣ ለእነርሱ የሚያስፈልጋቸው ለችግር ለተጋለጡትም የሚያስፈልጋቸው መሆኑን የተረዱ ናቸው። መስጠት ደስታን ሲሰጥ መቀበል ኃፍረትን ያላብሳል። መተባበርና መደጋገፍ ኃይል ሲፈጥር መለያየት ደግሞ አገርን ስለሚያዳክምና ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ መልካም ነው ተብሎ የተነገረውን ስለሚቃረን መተባበር ይገባል። ዘመኑ መደጋገፍና መረዳዳት የሚጠይቅ መሆኑን በመረዳት ከራስ ወዳድነት መላቀቅ ታላቅነት ነው። ቀያቸውን ለቀው የተሰደዱ፣ ሀብት ንብረታቸውን አጥተው በችግር የሚሰቃዩ፣ ወገኖቻቸው አልቀው በኀዘን የተጨበጡ ወገኖቻችን ቍጥር ከሚሊዮን በላይ ሆኗል። የተቸገሩትን መርዳት ሃይማኖታዊ ግዴታችን፣ ሥነ ምግባራዊ መገለጫችን መሆኑን ተረድተን ከሌሎቹ ቀድመን ለተቸገሩ ወገኖቻችን መድረስ የሚገባን ክርስቲያኖች ነን። አገራችን ሰላም ውላ እንድታድር ታላቅ ኃላፊነት እንዳለብን መዘንጋት የለብንም። መልካም በማድረግ የተጎዱትን የምንደግፈው በሌሎች ላይ የደረሰው መከራ እንዲደርስብን ስለማንፈልግ ብቻ ሳይሆን ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ በአምላኩ ዘንድ የሚመሰገን በመሆኑ ጭምር ነው። የሃይማኖት ልዩነት ሳንፈጥር ለተቸገሩ ወገኖቻችን ስንደርስላቸው በአንድ በኩል ክርስቲያናዊ አስተምህሯችን ለሌሎች ይገለጣል። ከዚህ በተጨማሪም ክርስቲያኖች የተቸገሩትን በመደገፋችን የሞራል ልዕልናችንን ዓለም ያውቀዋል። ሰዎች ሲቸገሩ ዓይተው የሚያዝኑ ክርስቲያኖች ንዑዳን ክቡራን ተብለው ተመስግነዋል። ወገኖቻችን አገር ለቀው ተሰደው፣ ቀያቸውን ትተው ተፈናቅለው እያየን ለእነርሱ የምናደርገው ድጋፍ ብቻ ሳይሆን ለእነርሱ ማዘናችን ንዑዳን ክቡራን ያሰኘናል ማለት ነው። በእርግጥ ክርስቲያኖች ለተቸገሩ ወገኖቻችን ሁሉ መልካም የምናደርገው ሰዎች ያመስግኑን፣ ንዑድ ክቡር ይበሉን ብለን አይደለም። ሰዎችን መደገፋችን አምላካችንን ስለሚያስደስተው ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ስንኖር አምላካችንን የሚያስደስት በጎ ምግባር መፈጸም ስላለብን ነው። መከራ ሲመጣ ደግሞ የበለጠ መተባበርና መደጋገፍ ይኖርብናል። የተፈጠርንለት ዓላማ ሠርተን ያገኘነውን ራሳችን በልተን እንድንደሰት ሳይሆን ሠርተን ካገኘነው ለሌላቸው ወገኖቻችን እንድናካፍል፣ ተባብረን ወገኖቻችንን ከሞት እንድንታደግ ነው። ተጋግዘን ለተቸገሩ ወገኖቻችን በመድረስ ሕይወታቸው እንድትቀጥል፣ ዕድሜ ለንስሓ ዘመን ለፍስሓ እንዲያገኙ ስናግዛቸው ደስታችን ፍጹም ይሆናል። በሃይማኖት የሚመስሉን ብቻ ሳይሆኑ የማይመስሉን ወገኖቻችንም በደረሰባቸው ችግር ምክንያት አገር ለቀው ሲሰደዱ፣ በስደት ወደ አሕዛብ አገር ሲሄዱ መታደግ ከክርስቲያኖች ሁሉ የጠበቅ ተግባር ነው። ለወገኖቻችን ራሳችንን ዐሳልፈን ለመስጠት የሚያስችል መንፈሳዊ ጥብዓት ባይኖረን እንኳ ከገንዘባችን ከፍለን ለተቸገሩ ወገኖቻችን መደገፍ ከሚጠበቅብን ክርስቲያናዊ ትሩፋት ትንሹ ነው። እስከ ሞት ድረስ የተቸገሩትን በመርዳት መታደግ፣ ሰውን ሁሉ መውደድ እንደሚገባን የተነገረን ለራሳችን ከሚያስፈልገን ቀንሰን ሌሎችም እንደሚያስፈልጋቸው አምነን እንድንረዳቸው ነው። እውነተኛ ወገን የሚታወቀው በመከራ ዘመን በመሆኑ አገር ለቀው ለተሰደዱ፣ በችግር አሽክላ ታስረው ለሚሰቃዩ፣ ረሃብና ኀዘን ተጨምሮባቸው ለሚንገላቱ ወገኖቻችን በመድረስ አለኝታነታችንን በተግባር እናሳያቸው። ከመንፈስ ልዕልና የደረሱት ሰዎች ለራሳችን ይቅርብን ብለው ወገናቸውን ሲያስቀድሙ እኛ ደግሞ ቢያንስ ካለን በማካፈል ለወገን አለኝታነታችንን እናረጋግጥ። በዘመናችንም ቅዱሳን ከፈጸሙት ያልተናነሰ ተግባር በመፈጸም ላይ የሚገኙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን የሚገልጠው ጦርነት በተነሣባቸው አካባቢዎች የሚገኙ አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ምእመናን የፈጸሙት ተግባር ነው። በጦርነት ምክንያት ቀያቸውን ለቀው የተሰደዱትን፣ በልዩ ልዩ ምክንያት ለችግር የተጋለጡትን ወገኖቻችንን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ የቋንቋም ሆነ የመልክአ ምድር ልዩነት ሳናደርግ መርዳት ከክርስቲያኖች ሁሉ የሚጠበቅ በጎ ተግባር ነው። በአሳብ አንድ ሆነን የወገን ፍቅር በልጦብን ተባብረን የተቸገሩትን ከደገፍን “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ”፤ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ፤ በተራራ ላይ የተሠራች ከተማ መሰወር አይቻላትም” ተብሎ የተነገረውን በተግባር ፈጸምን ማለት ነው። በክርስቲያናዊ ምግባራችን አልጫውን ዓለም ማጣፈጥ፣ ጨለማውን ዓለም ማብራት ሲገባ ገብር ሐካይ መሆን የለብንም።ክርስቲያኖች የተራራ ላይ ብርሃንና የምድር ጨው መሆናችን የሚገለጠው ሠርተን ካገኘነው ለወገኖቻችን ስንተርፍ ነው። ሰዎች ለመከራ በተጋለጡበት ዘመን የተቸገሩትን መረዳት ለተረጅዎች የሚኖረውን ጠቀሜታ ቃላት የመግለጥ አቅም የላቸውም። ተባብረን ወገኖቻችንን ስንረዳቸው ተጎጂዎች የሚያስብልን ወገን አለ ብለው ተስፋቸው ይለመልማል፤ ዙሪያው ገደል የሆነባቸው መውጫ መንገዱ ይታያቸዋል። ተስፋቸው መለምለም ብቻ ሳይሆን ተፈናቃዮች በደረሰባቸው መከራ ምክንያት በረሃብ እንዳያልቁ ያደርጋል። ልጆቻቸው ተርበው ሲያለቅሱባቸው ተስፋ ቆርጠው አምላካቸውን እንዳይክዱና ሃይማኖታቸውን እንዳይለውጡ የሚኖረው ጠቀሜታ ከፍተኛ በመሆኑ በመተባበር ወገኖቻችንን መርዳት ይኖርብናል። ተፈናቃዮች ዕድሜ ልካቸውን በሰው ድጋፍ ላለመኖርና ሠርተው ተለውጠው ራሳቸውን በመቻል ሌሎችን እንዲረዱም ተግባራዊ ትምህርት ያገኙበታል ብለን እናምናለን።
Thursday, 04 November 2021 00:00
ቸርነት፣ ደግነት፣ ምሕረትና ይቅር ባይነት የባሕርይ ገንዘቦቹ የሆኑት አምላካችን እግዚአብሔር በአምሳሉ የፈጠራቸው የሰው ልጆች ከመንገዱ በመውጣት በጠላት ወጥመድ ተይዘው እንዳይቀሩ “ወደ እኔ ተመለሱ” እያለ ዘወትር ይጠራቸዋል፡፡ ይህ ጥሪ የንስሓ ጥሪ ነው፡፡ ንስሓ መጸጸት፣ መቆጨት፣ በሠሩት ክፉ ተግባር ማዘን ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ንስሓ በሙሉ ልብ መመለስንና መለወጥን ያመለክታል፡፡ የሰው ልጅ ድካም የሚስማማውን ሥጋ እንደ መልበሱ ይደክማል፤ ይዝላልም፡፡ ከእውነት መንገድ፣ ከጽድቅ ሕይወት ወጥቶ ይስታል፡፡ ይሁን እንጂ የሚያስብ አእምሮና የሚያመዛዝን ሕሊና ያለው ፍጡር በመሆኑ የሠራውን ስሕተት አስተውሎ ይጸጸታል፡፡ ጸጸቱ የአሳብ ለውጥ መኖሩን ያመለክታል፡፡ ይህ የአሳብ ለውጥ ብቻ መፍትሔ አይሆንምና በተግባር መገለጥ አለበት፡፡ በአሳብም በተግባርም መለወጥ ማለት የንስሓ ጥሪን ተግባራዊ ማድረግ ነው፡፡ ጠቅለል አድርገን ስንመለከት ንስሓ እከብር ባይ ልቡና የሚያሳስበንን ሥጋዊ ፍላጎት ተከትለን፣ ስላጠፋነው ጥፋት፣ ስለበደልነውም በደል ምሕረትና ይቅርታ የምንጠይቅበት ለኃጢአትና ለጥፋት የጋበዘንን ሥጋችንን የምንገሥጽበት እና የምንቀጣበት፣ የእግዚአብሔርንም ቸርነት ደጅ የምንጠናበት ሥርዓት ነው፡፡ ስለዚህ ንስሓን ስናስብ ሦስት መሠረታዊ ነገሮችን መዘንጋት የለብንም። እነሱም፡- መናዘዝ፣ የሚሰጠንን ቀኖና መፈጸምና፣ ለኃጢአታችን ሥርየት የተሠዋልንን የክርስቶስን ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም መቀበል የሚሉት ናቸው። ፩. ኃጢአትን መናዘዝ የራስን ጥፋት አውቆ ለእግዚአብሔርም ለሰውም መናዘዝ የንስሓ የመጀመሪያው ደረጃ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አስተምህሮ መናዘዝ ስንል ሰው በአሳብ፣ በንግግር እና በተግባር በፈጸመው ኃጢአት ተጸጽቶ “እባክህ ከእግዚአብሔር ጋር አስታርቀኝ” ብሎ ጥፋቱን ለካህን ዘርዝሮ የሚናገርበት ሥርዓት ነው፡፡ አንድን ተነሳሒ እና ካህንን የንስሓ ልጅና አባት የሚያሰኘው ዋናው ጉዳይም ይህ ነው፡፡ የክርስቲያኖች የንስሓ አባት የመያዛቸው መሠረታዊ ዓላማም ይህ ነው፡፡ መናዘዝ የሚለውን ቃል ስናነሣ በሉቃስ ወንጌል የተጻፈውን የጠፋውን ልጅ ታሪክ ማስታወስ ይገባል፡፡ አንድ አባት ሁለት ልጆች ነበሩት፡፡ ከሁለቱ ልጆች መካከል ታናሹ ከአባቱ ንብረት የሚደርሰውን ተካፍሎ ለመውጣት ፈለገ፡፡ አባቱም ከሀብቱ ለልጁ ሊደርሰው ይገባል ያለውን ድርሻውን ከፍሎ ሰጠው፡፡ ልጁም ድርሻውን ተቀብሎ ወደ ሩቅ ሀገር በመሔድ ሀብቱን አባክኖ ጨረሰው፡፡ ኋላም በሚኖርበት ሀገር ጽኑ ራብ በሆነ ጊዜ ለአንድ ገበሬ የእሪያ ጠባቂ ሆኖ ተቀጠረ፡፡ ረሃብ ስለጸናበትም እሪያዎች ከሚበሉት አሰር ሊመገብ ቢፈልግም የሚሰጠውአልነበረም። ረሃብ ሲጸናበት “ወደ ልቡ ተመልሶ እንዲህ አለ፦ እንጀራ የሚተርፋቸው የአባቴ ሞያተኞች ስንት ናቸው? እኔ ግን ከዚህ በረሃብ እጠፋለሁ። ተነሥቼም ወደ አባቴ ልሔድ። አባቴ ሆይ፥ በሰማይና በፊትህ በደልሁ፥ ወደ ፊትም ልጅህ ልባል አይገባኝም፤ ከሞያተኞችህ እንደ አንዱ አድርገኝ እለዋለሁ” አለ፡፡ ወደ አባቱ ሲሔድ አባቱ ገና ሩቅ ሳለ አይቶ አዘነለት። ሮጦም አንገቱን አቀፈና ሳመው። ጎረቤቶቹንም ጠርቶ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይበለን ብሎ ታላቅ ድግስ ደገሰ ይለናል (ሉቃ.፲፭፥ ፲፩-፴፪)፡፡ ይህን አምላካዊ ቃል በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ መሠረት ሊቃውንት በብዙ መንገድ ያመሠጥሩታል፡፡ እኛ ግን አንዱን ብቻ ብንመለከት የሁለት ልጆች አባት የተባለው የሁሉ ፈጣሪና አባት እግዚአብሔር ነው፡፡ ሁለቱ ልጆች ደግሞ ቅዱሳን መላእክትና አዳም /የሰው ልጆች/ ፣ የጠፋው ታናሹ ልጅ የተባለውም አዳም ፣ ወደ ልቡ መመለሱ ደግሞ ንስሓ ለመግባት መወሰኑን፣ ጥፋተኛ ነኝና ልጅህ ልሆን አይገባኝም አገልጋይህ አድርገኝ ማለቱም ጥፋተኛነቱን አምኖ፣ ተጸጽቶ መናዘዙን ያስረዳልናል፡፡ የሰው ልጅ የለበሰው ሥጋ ለኃጢአት የሚስማማ ከመሆኑ የተነሣ ዕለት ዕለት አውቆ በድፍረት፣ ሳያውቅ በስሕተት እንዲሁም በቸልተኝነት ሕገ እግዚአብሔርን ይተላለፋል፡፡ በዚህም ምክንያት ከቤተ እግዚአብሔርና ከመንፈሳዊ አገልግሎት ይርቃል፡፡ ይህም የሕሊና ዕረፍት፣ የአእምሮ ሰላም፣ የልብ ደስታ እንዲሁም ሰማያዊ ርስትን የሚያወርስ ተስፋንም ያሳጣዋል፡፡ ያን ጊዜም ያዝናል፤ ይከፋል፤ ወደ ልቡም ተመልሶ መፍትሔ ይፈልጋል፡፡ መፍትሔውም ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቅ ሽማግሌ መፈለግ ነው፡፡ ይህ ሽማግሌም ካህን ነው፡፡ ካህኑም እንደ ሽማግሌነቱ ከእግዚአብሔር ጋር አስታርቀኝ ብሎ የመጣበትን ሰው አስታርቅህ ዘንድ ጥፋትህ ምንድን ነው ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ እርቅ ፈላጊውም ጥፋቱን (ኃጢአቱን) ዘርዝሮ ይናገራል፡፡ መናዘዝ የሚባለውም ይህ ነው፡፡ ኃጢአትን ለካህን የመናዘዝ ሥርዓት በኦሪት የነበረ፣ በወንጌል የቀጠለ ነው፡፡ ለምሳሌ በኦሪት “ወንድ ወይም ሴት የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ይተላለፍ ዘንድ ሰው የሚሠራውን ኃጢአት ቢሠራ በዚያም ሰው ላይ በደል ቢሆንበት በሠራው ኃጢአቱ ላይ ይናዘዝ” (ዘፀ.፭፥፮) ተብሎ ተጽፏል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ኃጢአትን ለካህን መናዘዝ እንደሚገባ ለምጻሞች ቀርበው ኢየሱስ ሆይ ማረን እያሉ ወደ እርሱ ሲመጡ “ወደ ካህን ሒዱና ራሳችሁን አስመርምሩ” በማለት ወደ ካህናት ልኳቸዋል፡፡ ሔደውም ራሳቸውን ለካህን ሲያስመረምሩ (ኃጢአታቸውን ሲናዘዙ) ከበደላቸው ነጽተዋል(ሉቃ.፲፯፥፲፪-፲፭)። ራስህን ለካህን አሳይ ያለውም ለምጽ በኃጢአት ምክንያት የሚመጣ በሽታ ስለነበረ (ዘሌ.፲፫፥፵፭-፵፮) ከጊዜያዊውም፣ ለዳግም ሞት ከሚያበቃው ሞትም እንዲድን ነው። ለኃጢአት በሽታ መድኃኒቱ ንስሓ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ፪. ቀኖናን ተቀብሎ መፈጸም ቀኖና (canon) የሚለው ቃል ምንጩ ጽርዕ (የግሪክ) ነው። ትርጓሜውም መቃ፣ መስፈሪያ፣ መለኪያ፣ መለካት መቊጠር ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፣ ፲፱፻፵፰፣ ገ.፯፻፺፱)። ከንስሓ ጋር በተያያዘ ያለው ትርጒም “አንድ ተነሳሒ በካህኑ ፊት ኃጢአቱን ከተናዘዘ በኋላ ካህኑ ለኃጢአት ማስተሥረያ የሚሰጠው የመንፈሳዊ ቅጣት መጠንና ዓይነት” ማለት ነው፡፡ ቀደም ብለን እንደተመለከትነው ሁሉ ካህኑ ኃጢአተኛውን ሰው ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቅ ሽማግሌ እንደ መሆኑ መጠን እርቁ እንዲፈጸም ጥፋተኛው ግለሰብ የሚጠበቅበትን መንፈሳዊ ግዴታ ለይቶ ማሳወቁ የማይቀር ነው፡፡ ምክንያቱም እርቅ ሲደረግ የበደለው አካል ይቅርታ ለማግኘት፣ የተበደለው አካል ደግሞ ይቅርታ ለማድረግ በየግላቸው ሊወጡት የሚገባቸው ድርሻ አለና፡፡ በዚህም መሠረት የተነሳሒ ድርሻ በፍጹም ልብ ከመመለስ በተጨማሪ የበደለውን መካስ፣ የቀማውን መመለስ እንዲሁም በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ በዕንባና በዋይታ ወደ እግዚአብሔር ማልቀስ ነው፡፡ ይቅርታ ማድረግ ግን ምሕረትና ቸርነት የባሕርይ ገንዘቡ የሆነው የእግዚአብሔር ነው፡፡ ካህኑ ለኃጢአተኛው ሰው እግዚአብሔር ይቅር ይልህ ዘንድ መንፈሳዊ ተግባራትን ፈጽም ብሎ የሚያዝዘው ትእዛዝ ቀኖና ይባላል፡፡ ይኸውም በብሉይ ኪዳን የኃጢአት፣ የበደል፣ የደኅንነት ወዘተ. መሥዋዕት ተብለው የፍየል፣ የበግ፣ የርግብ ወዘተ መሥዋዕት በማቅረብ ይፈጸም የነበረ ሲሆን በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ጹም፣ ጸልይ፣ ስገድ፣ መጽውት የሚለው መጠን እንደካህኑ ሁኔታ የሚወሰን ይሆናል፡፡ ቀኖና በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊ አስተምህሮ መሠረት ሰው ከስሕተቱ የሚታረምበት መንፈሳዊ ተግሣጽ ሲሆን ይህ ግን ምድራውያን ነገሥታት ለወንጀለኞች እንደሚሰጡት ቅጣት የሚታይ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ይቅር የሚለው ኃጢአተኛነቱን አምኖ በማዘኑ፣ በመቆጨቱና ከጥፋቱ በመመለሱ እንጂ ስለበደሉ በሚከፍለው ካሳ ብዛት አይደለምና፡፡ ለዚህም ቀደም ብለን ባየነው የጠፋው ልጅ ታሪክ ላይ ልጁ ለመናዘዝ ወደ አባቱ እየመጣ ሳለ “አባቱ ግን ገና ሩቅ ሳለ አየውና አዘነለት፥ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው” (ሉቃ.፲፭፥፳) የሚለው የሚያሳየው የአባቱን ርኅራኄ እንጂ ቀኖናው ከኃጢአቱ አቻ መሆኑን አይደለም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ “የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና” (፩ኛ ጴጥ.፬፥፫) ባለው መሠረት ነው።አባቶቻችንም ይህንን መሠረታዊ ትምህርት አብነት አድርገው ኃጢአተኛው በኃጢአት ባሳለፈበት ዘመን ፈንታ ቀሪ ዘመኑን በጽድቅ ጎዳና እንዲመላለስ የሚያበቃውን ቀኖና ይሰጡታል፡፡ ሐዋርያው “የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና” በማለት መናገሩ ከተመለሳችሁ ይበቃል ማለቱ አይደለም፡፡ በኃጢአት ፈንታ ፈቃደ እግዚአብሔርን ፈጽሙ ማለቱ እንጂ፡፡ አባቶች ካህናትም በዚሁ መሠረት ለኃጢአተኛ ሰው በቀማህበት ፈንታ መጽውት፣ ያለ ልክ በመብላትና በመጠጣት፣ በስካር፣ በኃጢአት ባሳለፍክበት ዘመን ፈንታ ጹም፣ ጸልይ፣ ስገድ በማለት ለኃጢአተኛው ቀኖና የሚሰጡት መንፈሳዊውን ጣዕም እንዲቀምስ ነው፡፡ እንዲያውም አባቶቻችን ለባለጸጋ ጾምን፣ ምንም ለሌለው ድሃ ምጽዋትን በማዘዝ ኃጢአተኞች ፈቃደ እግዚአብሔርን ለመፈጸም በሰውነታቸው ላይ ጨክነው መወሰንን እንዲለማመዱ ያዛሉ፡፡ ምክንያቱም ለባለጸጋ ምግብ በቤት ውስጥ ሞልቶ ተርፎ እያለ መጾም፣ ለድሃ ደግሞ ቆጥቦ ያስቀመጠውን ወይም ለምኖ ያገኘውን ገንዘብ መመጽወት ከባድ ነውና፡፡ ይሁንና ድሃ ጦሙን አድሮም ቢሆን ይመጸውታል፤ ባለጸጋም ለተወሰነ ቀን ነውና እንደምንም ራቡን ታግሦ ይጾማል፡፡ ከዚህም የተነሣ ሰውነታቸው ኃጢአትን ከመጸየፍ በተጨማሪ ለጽድቅ መታዘዝንም ይለማመዳል፡፡ ስለዚህ ተነሳሕያን የሚሰጣቸውን ቀኖና በዛ ብለው ሳያንጎራጉሩ፣ አነሰም ብለው ሳይጠራጠሩ በካህኑ ቀኖና ላይ የእግዚአብሔር ቸርነት እና የተነሳሒው ትሩፋት ተጨምሮበት ከታላቅ በደልና ኃጢአት እንደሚያነፃቸው አምነው ቀኖናቸውን ተቀብለው መፈጸም ይገባቸዋል፡፡ ፫. ሥጋውንና ደሙን መቀበል በክርስትና አስተምህሮ የአገልግሎቶች ሁሉ መደምደሚያው ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ነው፡፡ የካህናትና የመምህራን መሾም ዋና ግቡ ምእመናንን አስተምረው ለሥጋውና ለደሙ ማብቃት ነው፡፡ ምክንያቱም የመንፈሳዊ አገልግሎት ሁሉ ግቡ ሰማያዊ ርስት መውረስ ነውና፡፡ ያለክርስቶስ ሥጋና ደም ደግሞ ሰማያዊ ርስት ማለትም የዘለዓለም ሕይወት የለም፡፡ ምክንያቱም “..እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ፤ ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ ሕይወት የላችሁም” (ዮሐ.፮፣ ፶) ተብሎ ተጽፏልና፡፡ በጠፋው ልጅ ታሪክ አስቀድመን እንደተመለከትነው ልጁ ወደ አባቱ ቤት ሲመለስ አባቱ ፍሪዳ አርዶ፣ ድግስ ደግሶ ተቀብሎታል፡፡ የጠፋው ልጅ አዳም ነው፡፡ የጠፋውን አዳምን ፍለጋ የመጣው ደግሞ ክርስቶስ ነው፡፡ “የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቷልና” (ሉቃ.፲፱፥፲) እንዲል፡፡ ለአዳም ልጆች የሕይወት ምግብ ሊሆን የታረደው ፍሪዳም ራሱ ክርስቶስ ነው፡፡ በቀራንዮ ኮረብታ በዕለተ ዓርብ በመስቀል ተሰቅሎ ሥጋውን ቆርሶ፣ ደሙን አፍስሶ መሥዋዕት ሆኗልና፡፡ ጌታችን በዕለተ ዓርብ መሥዋዕት ከመሆኑ አስቀድሞ ሐሙስ ማታ “እንጀራን አንሥቶ ባርኮ ቈርሶ እንካችሁ ብሉ ይህ ሥጋዬ ነው፤ እንዲሁም ጽዋውን አንሥቶ አመስግኖ ሁላችሁ ከእርሱ ጠጡ፤ ስለብዙዎች ለኃጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው” (ማቴ.፳፮፥፳፮) በማለት ለደቀ መዛሙርቱ ሰጥቷቸዋል፡፡ ይህም የክርስቶስ ሥጋና ደም ለእኛ የሕይወት ምግብና መጠጥ ሆኖ መቅረቡን የሚናገር ነው፡፡ ስለዚህ እኛም የዘለዓለም ሕይወት ለማግኘትና ሰማያዊ ርስትን ለመውረስ የክርስቶስን ሥጋና ደም መቀበል ይኖርብናል፡፡ “ሥጋዬን የሚበላ፣ ደሜንም የሚጠጣ በእኔ ይኖራል፤ እኔም በእርሱ እኖራለሁ። ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ የተነሣ ሕያው እንደምሆን፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል” (ዮሐ.፮፥፶፮-፶፯) የሚለውም ይህንኑ የሚያስገነዝበንነው፡፡ በኦሪቱ በነበረው የመሥዋዕት ሕግ እስራኤላውያን የፋሲካውን በግ ሲመገቡ ጫማቸውን ተጫምተው፣ ወገባቸውን ታጥቀው፣ ኩፌታቸውን ደፍተው በትራቸውን ይዘው እየተቻኮሉ እንዲመገቡ ታዘው ነበር (ዘፀ.፲፪፥፲፩)፡፡ ይህም ዛሬ ላለነው ክርስቲያኖች ምሳሌ ሆኖን የአማናዊውን በግ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋውንና ደሙን ስንቀበል በጎ ምግባር ሠርተን፣ ወንጌሉን ተጫምተን፣ የንጽሕናን ዝናር ታጥቀን፣ አክሊለ ሦክን፣ ነገረ መስቀሉን እየዘከርን (መስቀሉን ተመርኩዘን)፣ ሞት እንዳለብን በማሰብ እንዳይቀድመን ፈጥነን ንስሓ በመግባት ሥጋውንና ደሙን መመገብ የሚገባን መሆኑን ያስገነዝበናል፡፡ ቀደም ብለን ባየነው የጠፋው ልጅ ታሪክም አባት ልጁ ከጠፋበት ሲመለስ ፊሪዳውን ከማረዱ በፊት “ባሪያዎቹን ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፥ ለእጁ ቀለበት፣ ለእግሩም ጫማ ስጡት” በማለት ልጁ ታጥቦ ንጹሕ የሆነውን ልብስ ለብሶና አዲስ ጫማ ተጫምቶ እንዲዘጋጅ ነበር ያደረገው፡፡ ልጁን ወደ ልቡ እንዲመለስና የአባቱን ቤት እንዲያስብ ያደረገው ረሃብ ነበር፡፡ “እንጀራ የሚተርፋቸው የአባቴ ሞያተኞች ስንት ናቸው? እኔ ግን ከዚህ በራብ እጠፋለሁ አለ” በማለት መናገሩ ምስክር ነው፡፡ ከአባቱ ቤት ካለው ማዕድ ለመቀበል ግን አስቀድሞ ያንን ማዕድ አቋርጦ በመውጣት የበደለውን አባቱን ይቅርታ መጠየቅ ነበረበት፡፡ ስለሆነም አባቱን ማረኝ አለው፡፡ አባቱም ይቅር አለው፡፡ ከዚያ በኋላ ከፊሪዳው ተመገበ፡፡ እኛም ገና በአርባና በሰማንያ ቀናችን ጀምረን ስንመገብ የኖርነውን ሥጋውንና ደሙን መቀበል አቋርጠን ወደ ተለያየ የኃጢአት ሕይወት ብንገባም እንኳ ወደ ልባችን ተመልሰን ሥጋውንና ደሙን ለመቀበል ስንመጣ አስቀድመን ስለጥፋታችን ይቅርታ መጠየቅ እንደሚገባን ያስገነዝበናል፡፡ ይህም ሥጋውንና ደሙን ለመቀበል ንስሐ ገብተን መዘጋጀት የሚገባ መሆኑን ይገልጣል። አንድም የንስሓ ጉዞ መጨረሻው በክርስቶስ ሥጋና ደም መታተም የሚገባው መሆኑን እንድንገነዘብ ያደርገናል፡፡ በአጠቃላይ ሰው በኃጢአቱ ምክንያት ከእግዚአብሔር ከተለየ በንስሓ መመለስ ይኖርበታል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችንም በነቢዩ ላይ አድሮ አምላካዊ ጥሪውን ያስተላለፈውና “ወደ እኔ ተመለሱ” እያለ የሚጠራን ለንስሓ ነው፡፡ ስለሆነም ሁላችንም በንስሓ ወደ እግዚአብሔር ተመልሰን፣ ቅዱስ ሥጋውን በልተን፣ ክቡር ደሙን ጠጥተን ከቅዱሳን ማኅበር እንዲጨምረን የሚጠበቅብንን መወጣት አለብን፡፡ በንስሓ ተመልሰን በቤቱ እንድንኖር እግዚአብሔር በቸርነቱ፣ ቅዱሳን በአማላጅነታቸው አይለዩን። አሜን!!   

ማስታወቂያ