Search results for: ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ - ሐመረ ጽድቅ
 ክህነት እንዴት ይሾማል   ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ “ኢኀደጋ ለምድር እንበለ ካህናት ወዲያቆናት፣ እምቅድመ ዓለም ወእስከ ለዓለም፤ ቸሩ አምላክ እግዚአብሔር ለዘለዓለም እስከ ለዓለም ምድርን ያለ ካህናትና ዲያቆናት አልተዋትም’’ (ዚቅ ዘኅዳር ጽዮን) በማለት እንደገለጸው ክህነት ከጥንት ከአዳም ጀምሮ እንደነበረ በክፍል አንድ ተመልክተናል፡፡ በዚህ ክፍል ደግሞ ክህነት እንዴት ይሾማል የሚለውን እንመለከታለን፡፡ የክህነት አሿሿም ሥርዓት በየዘመናቱ ይለያያል፡፡ ሿሚው ራሱ እግዚአብሔር ሁኖ የሚሾምበት ሥርዓት ግን እንደዘመናቱ ነባራዊ ሁኔታ የተለያየ እንደነበር መገንዘብ ይገባል፡፡ ለምሳሌ አዳምን በቀጥታ እግዚአብሔር ሾመው፤ መልከ ጼዴቅንም እንዲሁ በቀጥታ እግዚአብሔር ሾመው፡፡ አሮንና ከእርሱ በኋላ የነበረውን የክህነት አሿሿም ስንመለከት ደግሞ በሙሴ አማካኝነት ተሾሙ:: ከዚያ በኋላ በዘር ማለትም ከሌዊ ወገን የሆነውን በዘመኑ የሚኖረው ሊቀ ካህን ሲሾም ኖሯል፤ ሐዋርያትን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሾማቸው፤ ከእነርሱ በኋላ ደግሞ ተከታዮቻቸውን እነርሱ እንዲሾሙ ታዝዘዋልና ሐዋርያት ሲሾሙ ኖረዋል፤ የእነርሱ ተከታዮችም እንዲሁ እየሾሙ ኖረዋል፡፡ የሐዲስ ኪዳኑ አማናዊ ክህነት ከሐዋርያት ጀምሮ ሐዋርያዊ ቅብብሎሹ ሳይቋረጥ እየተላለፈ ዛሬ ላይ ደርሷል፡፡