Saturday, 25 September 2021 00:00

አሜሪካ ዓለም አቀፍ የኦርቶዶክሳውያንን አንድነት ለመናድ አቅዳ እየሠራች መሆኑ ተገለጠ

Written by  ካሳሁን ለምለሙ

Overview

አሜሪካ በኦርቶዶክሳውያን መካከል ያለውን አንድነት ለመናድ አቅዳ እየሠራች መሆኑን የሩሲያው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ሚስተር ሰርጌ ላቭሮቭ መናገራቸውን ኦርቶዶክስ ኮግኔት ፔጅ አስነበበ፡፡ አሜሪካ በሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ላይ ከፍተኛ ጫና እያደረሰች መሆኗን የገለጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒሰቴሩ በኮኒስታንቲኖፕል ሀገረ ስብከት አፍራሽ ሚና በመጫወት የዩክሬን ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን ለመክፈል  ከፍተኛ ጥረት እያደረገች መሆኑንንም አንስተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ምዕራባውን በተለይም አሜሪካ በሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ጫና እያሳደሩባት መሆኑን ያጋለጡት ሰርጌ ላቭሮቭ “ዓላማቸውም የዓለም ኦርቶዶክሳውያንን አንድነት ለማጥፋት ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡  ምዕራባውያን በኮኒስታንቲኖፕል የዩክሬን ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን ለመክፈል የተጠቀሙትን መንገድ በቤላሩስና በሜዲትራሊያን ሀገሮች ላይ በዋናነትም ሶርያን፣ የሊባኖስን እንዲሁም ባልካንን በመቆጣጠር የሰርቢያ ኦርቶዶክስ  ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት አቅደው እየተንቀሳቀሱ መሆኑን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ አስታውቀዋል፡፡  የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴሩ አያይዘውም መሥሪያ ቤታቸው የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን ባህል፣ ዕሴትና ለሩሲያ የውጭ ግንኙነት እያበረከተች ያለችውን አስተዋጽኦ እያስተዋወቀ መሆኑን ገልጠው ይሁን እንጅ የቤተ ክርስተያኗ የቀደመ ትውፊት “ሃይማኖት አያስፈልግም” በሚሉ የምዕራባውያን ሊሂቃን  እየተፈታነ መሆኑንም አክለዋል፡፡   
Read 359 times