Tuesday, 23 February 2021 00:00

“የአንገት ማዕተቤን አላወልቅም” ያለው ወጣት ከሥራ ገበታው ተሰናበተ

Written by  ካሳሁን ለምለሙ

Overview

ኗሪነቱን ስዊድን ያደረገው የሃያ ስምንት ዓመቱ ጆርጅ ታኑዋሪ ‹‹የአንገት ማዕተቤን አላወልቅም›› በማለቱ ከሥራ ገበታው ተሰናበተ።  የሶሪያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታይ የሆነው ጆርጅ ተቀጥሮ ከሚሠራበት ድርጅት የአንገት ማዕተቡን እንዲያወልቅ ተጠይቆ በመቃወሙ ምክንያት ከሥራ ገበታው እንደተሰናበተ ኦርቶዶክስ ኮግኔት ፔጅ አስነብቧል።     ወጣቱን ቀጥሮ የሚያሠራው “ኢንግራም ማይክሮ” የተባለው ድርጅት “አንገት ላይ መስቀል ማድረግ ለደኅንነት አደገኛ ነው” ብሎ በማመኑ ወጣቱ መስቀሉን እንዲያወልቅ ቢጠይቀውም ወጣቱ በመቃወሙ ከሥራ ገበታው እንዳሰናበተው ከዘግባው ለመርዳት ተችሏል። በርካታ የእስልምና እምነት ተከታይ ጓደኞቹ ጀለቢያና ሂጃብ አድርገው እየሰሩ እርሱ ማዕተብ እንዳያደርግ መከልከሉ ሃይማኖታዊ መድሎ እንደተፈጸመበት መሆኑን ማስረዳቱን በዘገባው ተገልጧል።     የኩባንያው ባለሥልጣናት በበኩላቸው መስቀልም ሆነ ጌጣጌጥ ማድረግ እንደማይፈቀድ ለወጣቱ ማስረዳታቸውን ገልጸዋል። ጆርጅ በበኩሉ በድርጅቱ ተቀጥረው  ያሉ ሠራተኞች ጌጣጌጦችንና የእስልምና አልባሳትን ለብሰው ሲሰሩ ማየቱን ገልጾ ‹‹በድርጅቱ ተቀጥረው ያሉ ሌሎች ብዙዎች ሂጃብ ለብሰው እንደሚሠሩት ሁሉ እርሱም የአንገት መስቀል በአንገቱ ላይ አድርጎ የመስራት መብት እንዳለው ለኩባንያው ባለሥልጣናት ማስረዳቱን ዘገባው አመላክቷል።     ባለፉት ዓመታት በምእራብ አውሮፓ ሀገራት በክርስቲያኖች ላይ በርካታ የሃይማኖት መድሎዎች መደረጋቸውን አስመልክቶ ሪፖርት መደረጉን ዘገባው አመልክቷል።     
Read 535 times