Wednesday, 28 April 2021 00:00

የማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ አገልጋዮች የመቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከልን ጎበኙ . ከቁሳዊ ድጋፍ በተጨማሪ መንፈሳዊ ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ተገለጸ

Written by  በጋዜጣው ሪፖርተር

Overview

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት ማደራጃ መምሪያ የማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ አገልጋዮች ሚያዚያ ፩ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም መቄዶንያ የአረጋውያንና  የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከልን በመጎብኘት የመቊረቢያ አልባሳትንና የጸሎት መጻሕፍትን ለገሱ።    የጉብኝት ጉዞው አስተባባሪ የሆኑት አቶ ግሩም አሥራት ‹‹የታመሙትን መጠየቅ፣ የተቸገሩትንም መርዳት ግዴታችን ነውና ለአረጋውያኑና ለአእምሮ ሕሙማኑ ከቁሳዊ ድጋፍ ባሻገር መንፈሳዊ ድጋፍ ልናደርግላቸውው ይገባል››  ብለዋል። አስተባባሪው አክለውም ‹‹በቃል የምናስተምረውን በተግባር ማሳየት ይጠበቅብናል›› ሲሉ ተናግረዋል። በቀጣይም የቀሩትን  የማኅበረ ቅዱሳንን አባላት በማሳተፍ ድጋፍ እንደሚያደርጉ ገልጸዋል። በማዕከሉ የተገኙት የማኅበሩ መደበኛ አገልጋይ ቀሲስ ይግዛው መኮንን በበኩላቸው ‹‹መስማት ማየትን አይተካውም የምንሰማውና የምናየው የተለያየ ነው ፤ እኔ እስከዛሬ ስለ ማዕከሉ ሳልሰማ ቀርቼ አይደለም  ፤ ነገር ግን በፊት ከነበረኝ አመለካከት ዛሬ ብዙ ነገር ተምሬአለሁ ፤ መማር ብቻ ሳይሆን ብዙ ነገር ለማድረግ ወስኛለሁ፤ ስዚህ ሌሎቻችንም በአካል መጥተን ማዕከሉን አልናይ ይገባል።›› ብለዋል።  አረጋውያኑም የማኅበሩ አገልጋዮች ማዕከሉ ድረስ በመሄድ ስላደረጉላቸው ድጋፍ ልባዊ ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን የማዕከሉ መሥራች  ክቡር ዶክተር ብንያም በለጠም ‹‹አረጋውያኑን እና የአእምሮ ሕሙማኑን ስለጠየቃችኋቸው፣ ድጋፍም ስላደረጋችሁላቸው ልባዊ ምስጋናዬን አቀርባለሁ ›› ያሉ ሲሆን በመቀጠልም ‹‹የቤተ ክርስቲያን አባቶች መጥተው እንዲረዱን እንዲሁም  ፹፩ ፷፩ ላይ OK ብለው በእጅ ስልካቸው ላይ በመላክ እና አንድ ብር በመስጠት ጎዳና ላይ የወደቁ  ወገኖቻችንን እናነሳ ዘንድ በእናንተ በኩል አስፈላጊውን ትብብር እንድታደርጉል›› ሲሉ መልእክታቸውን አስተላለፈዋል። 
Read 469 times